የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ 15ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል እና 18ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሄደ::
ነሐሴ 26 ቀን 2018 ዓ.ምየኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ 15ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል እና 18ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ ስካይ ላይት ሆቴል አካሂዷል።
በዚህ ታላቅ ጉባኤ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ክብሩ አምባሳደር ታዬ አጽቀ ሥላሴ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ተወካይ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳምና ሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ጠባቂ፤ ብፁዕ አቡነ መልኬጸዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት እና የአቡነ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ፤ ፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች የተለያዩ የቤተክርስቲያን ተወካይ አባቶች ፤ የልዩ ልዩ የሃይማኖት ተቋማት ተወካዮች እና ሥራ አስፈጻሚዎች፤ የክልል እና የአዲስ አበባ ተወካዮች፤ የተቋሙ የቦርድ አባላት እንዲሁም የዓለም አቀፍ ተቋማት ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።
መርሐ ግብሩ በሃይማኖት አባቶች የመክፈቻ ጸሎት የተጀመረ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት የ15 ዓመታት የጉዞ ታሪክ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም ቀርቧል።

በተጨማሪም ጉባኤው ባሳለፋቸው 15 ዓመታት ከጎኑ በመቆም በአህጉራዊ ሰላምና ፀጥታ ዙሪያ፣ በሰብአዊ መብቶች እና በሴቶች ዙሪያ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን አብረው ሲያከናውኑ የቆዩ እንደ UNICEF (ዩኒሴፍ) እና ሰተርሊንግ ፋውንዴሽን ያሉ በርካታ ዓለም አቀፍ አጋር ተቋማትና ተወካዮች፣ ወደፊት በሚያከናወኑት አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተልዕኮዎች ላይ ገለጻ በማድረግ የ15 ዓመታት ሰላማዊ የአብሮነት ጉዞን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ጸሐፊ ሊቀ ትጉኀን ቀሲስ ታጋይ ታደለ በበኩላቸው፣ ጉባኤው በይፋ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ አባል የሃይማኖት ተቋማት ከመንፈሳዊ አገልግሎታቸው ጎን ለጎን በሀገራዊ የሰላምና የልማት ጉዳዮች ላይ የድርሻቸውን እንዲያበረክቱ የማቀድ፣ የማስተባበርና የማመቻቸት ሥራዎችን ሲሠራ መቆየቱን ገልጸዋል።
አክለውም ከመንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ሀገር በቀልና ዓለም አቀፍ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የሰላምና የመከባበር የጋራ እሴቶች እንዲጠበቁ ሃይማኖታዊ አስተምህሮን መሠረት ያደረጉ የግንዛቤና የአብሮነት ሥራዎች በሀገር አቀፍ፣ በክልልና በከተማ አስተዳደሮች ደረጃ ሲከናወኑ መቆየታቸውንና አሁንም እየተሠሩ መሆኑን አብራርተዋል።
የሰላም ሚኒስትር ክቡር አቶ መሐመድ ኢድሪስ ባስተላለፉት መልእክት፣ በ15 ዓመታት ውስጥ በየደረጃው የተካሄዱ መድረኮች የልዩ ልዩ ሃይማኖት ተከታይ የሆኑ ኢትዮጵያውያን የእርስ በእርስ አስተምህሮን እንዲረዱ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ገልጸዋል።
ሚኒስትሩ አክለውም እንዲህ ዓይነቱ ጉባኤ የሃይማኖት ተቋማት የጋራ ፍላጎቶችንን የምናሰፍንበት፣ እምነትን በተግባር የምናጸናበትና የአብሮነትን ታላቅ ቁምነገር የምናሳይበት፣ ባለፉት 15 ዓመታት የሕዝባችንን የሞራልና የስነ-ምግባር እሴቶች ሲቀርጹ የነበሩ የዕድገት ምሳሌዎች መሆናቸውን በመጠቆም፣ በቀጣይም “ለሃይማኖትና ለሀገር የማይሆን ዜጋ እንዳንፈጥር በርትተን ከዘመኑ ጋር በመፍጠን ልንሠራ ይገባል” ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።
በመጨረሻም ለጉባኤው ስኬት የሙያዊና የፋይናንስ ድጋፍ ላደረጉ ተቋማትና ግለሰቦች በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ እና በሌሎች የሃይማኖት መሪዎች አማካይነት የዕውቅና ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
©የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/