በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የታቦር ፍኖተ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ለሁለተኛ ዙር አስመረቀ።
ሰኔ 27 ቀን 2018 ዓ.ምሀዋሳ-ኢትዮጵያ
በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የምዕራብ ሽዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣መጋቤ ጥበባት አባ ዘሚካኤል የሲዳማ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የወረዳ ሊቃነ ካህናት፣የገዳማትና የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶችና የሀገር ሽማግሌዎች፣ተመራቂ ደቀ መዛሙርትና የተመራቂ ደቀ መዛሙርት ቤተ ሰቦች ተገኝተዋል።
በእለቱ ለብፁዓን አባቶችና ለእንግዶች የእንኳን ደና መጣችሁና ለተመራቂ ደቀ መዛሙርት የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት ያስተላለፉት ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የታቦር ፍኖተ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ ”ወናሁ አነ እፌንዎክሙ ከመ አባግዕ ማዕከለ ተኩላት” / ማቴ 10፥16 /
ያለውን በማንሳት ሰፊ መልእከት አስተለላፈዋል።
በመቀጠል በኮሌጁ ዲን በመጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ ነጻነት አክለወግ ሪፖርት ቀርቧል። በሪፖርታቸው የምናቀርበው የታማሪዎችን ውጤት ብቻ ሳይሆን የአባቶቻችን የሊቃነ ጳጳሳት የወደ ፊት ራዕይና የአመራር ብቃት፣የመምህራን ጥረት ነው።
ዛሬ ለሁለተኛ ዙር እያስመረቀ ያለው ኮሌጅ ለረዥም ጊዜ በካህናት ማስለጠኛነት የቆየ ሲሆን በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ከፍተኛ ጥረትና በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ በ2015 ዓ/ም ሥራውን የጀመረ ሲሆን ዛሬ በመደበኛው ለሁለተኛ ዙር 12 ፣ በማታ ለመጀመሪያ ጊዜ 20 ፣በቅዳሜና እሑድ ለመጀመሪያ ጊዜ 45 በድምሩ 77 ከእነዚህ መካከል ስድስት ሴቶች ይገኙበታል።
ይህ የሚያሳየው ለመደበኛ ደቀ መዛሙርት የሚሰጠው ትምህርት እንዳለ ሆኖ በማታና በእረፍት ቀናት ከቤተሰብ ሳይለዩ የሚማሩበት እድል መፈጠሩን ማሳያ ነው ብለዋል።
በመቀጠል ለሁሉም ተመራቂ ደቀ መዛሙርት ባይንደር በብፁዓን አባቶች ተሰጥቶ ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ደቀ መዛሙርት ሽልማት ከተሰጠ በኋላ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሊቀ ጳጳስ “መከሩ ብዙ ነው ሠራተኞች ግን ጥቂት ናቸው” /ማቴ 9፥37/ ዛሬ የተመራቃችሁ ደቀ መዛሙርት ዛሬም መከሩ ብዙ ሠራተኛች ጥቂት በመሆናቸው ለቤተ ክርስቲያን ተጨማሪ ጉልበት ናችሁ። ዓለምን ያጣፈጡት የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ሦስት ዓመት ከክርስቶስ ሥር ቁጭ ብለው ተመረው በጆሯቸው የሰሙትን በዓይናቸው ያዩትን መስክረዋል።
ዛሬም እናንተ በቆያችሁባቸው ሦስት ዓመታት በጆሯችሁ የሰማችሁትን በዓይናችሁ ያያችሁትን እንድትመሠክሩ ነው።
ዛሬ እንደ እናንተ በዓላማዊ የሚመረቁ አሉ ለምን ሥጋዊውን ዓለም ለማገልገል ነው እናንተ ደግሞ በዓለማዊው ዓለም ለመንፈሳዊው ዓለም እንድታገለግሉ ነው።
ስለዚህ አሁንም ክርስቶስ በዚያን ጊዜ እንደተናገረው በዓለም ካለው ሕዝብ አንጻር የሠራተኛው ቁጥር ጥቂት ነው።
በአጠቃላይ የእናንተ ጥሪ ለሹመት ለሽልማት ባለመሆኑ የተጣለባችሁን እንድትወጡ አደራ ብለዋል።
በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ መቃርዮስ የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ጸሎትና ቡራኬ የፕሮግራሙ ፍጻሜ ሆኗል።
© ኢዮር ሚዲያ ሲዳማ ሀገረ ስብከት