የቤተ ክርስቲያን የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች ሥልጠና በአሰልጣኞች ማጠቃለያ ሁለተኛ ቀኑን አጠናቀቀ
(ሐምሌ ፲ ቀን ፪ሺ፲፰ ዓ.ም.፤ አዲስ አበባ)፦ “የሕዝብ ግንኙነት ስኬት ለቤተክርስቲያን አገልግሎት” በሚል መሪ ቃል በጁፒተር ኢንተርናሽናል ሆቴል የተዘጋጀው የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች ሥልጠና ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዞ ውሏል።በኢኦተቤክ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በተዘጋጀው በዚህ ሀገር አቀፍ መድረክ ላይ በትላንትናው ዕለት (ሐምሌ ፱ ቀን) በምሁራን አማካኝነት ዋና ዋና የሙያ ትምህርቶች ተሰጥተው የነበረ ሲሆን፣ ዛሬ በሁለተኛው ቀን (ሐምሌ ፲ ቀን) ደግሞ በአሰልጣኞቹ ሰፊ ማጠቃለያና ሙያዊ ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል።
በትላንትናው ዕለት ቀርበው ዛሬ በማጠቃለያው መድረክ ላይ በሰፊው የተዳሰሱት ዋና ዋና የሥልጠና ርዕሰ ጉዳዮች የሚከተሉት ናቸው፦
“በቤተ ክርስቲያን የሕዝብ ግንኙነት ምንነትና እሴቶች” (በአቶ ነጻነት ተስፋዬ)፦ የሕዝብ ግንኙነት ሥራ ከተራው ዓለማዊ መዋቅር በተለየ መልኩ መንፈሳዊ እሴቶችን፣ እውነትንና ታማኝነትን መሠረት አድርጎ እንዴት መዋቀር እንዳለበትና የሙያው መሠረታዊ ምንነት በስፋት ቀርቧል።
“ኦርቶዶክሳዊ የቀውስ ጊዜ ተግባቦት” (በዲ/ን ታደሰ ወርቁ)፦ ቤተ ክርስቲያን ከተለያዩ አቅጣጫዎች የሚሰነዘሩባትን ተግዳሮቶችና ወቅታዊ ቀውሶች (Crises) በበሰለ፣ በተደራጀና ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓትን በጠበቀ መልኩ የመረጃ ፍሰቱን በመምራት እንዴት መመከት እንዳለባት የሚያስገነዝብ ስልታዊ ትንታኔ ተሰጥቶበታል።
“ዲጂታል ኮሙዩኒኬሽንና የማኅበራዊ ሚዲያ አያያዝ” (በዶ/ር ዘሩ ብርሃነ)፦ በቴክኖሎጂው ዘመን ማኅበራዊ ሚዲያዎችን ለተቋማዊ ስኬትና ለወንጌል አገልግሎት ማዋል በሚቻልበት፣ የሐሰት ትረካዎችን በዲጂታል መንገድ መከላከልና ዘመናዊ የመገናኛ ዘዴዎችን በአግባቡ ስለመጠቀም የሚያስረዳ ሙያዊ ማብራሪያ ቀርቧል።
በዛሬው የሁለተኛ ቀን ውሎ አሰልጣኞቹ በትላንትናው ዕለት በቀረቡት በእነዚህ ሦስት ዋና ዋና አጀንዳዎች ላይ ያቀረቡት ማጠቃለያ የባለሙያዎችን አቅም ለመገንባት፣ ወቅታዊ ተግዳሮቶችን ለመመከትና ዘመናዊ የመገናኛ ዘዴዎችን በመጠቀም የመረጃ ክፍተቶችን ለመሙላት ትልቅ መሠረት የጣለ መሆኑ ተገልጿል።