የቅድስት ልደታ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በዲግሪ መርሐ ግብር እና በቴክኒክ እና ሙያ ሥልጠና ያስተማሯቸውን ተማሪዎች አስመረቀ።
ሐምሌ 11 ቀን 2018 ዓ.ምየቅድስት ልደታ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በተለያዩ የዲግሪ መርሐ ግብራት በጤና ሳይንስ እና ሌሎች ዘርፎች ያስተማራቸውን ተማሪዎቹን ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ስብሐት አባ ገብረ ሥላሴ በተገኙበት አስመርቋል።
ኮሌጁ በዲግሪ 460 ፤ በቴክኒክና ሙያ ሥልጠና 343 በጠቅላላው 803 ተማሪዎችን ነው ያስመረቀው።
ኮሌጁ እስካሁን ለ18 ጊዜ ተማሪዎችን ያስመረቀ ሲሆን ፤ በጤናና በቴክኒክ ዘርፎች ብቁ ባለሙያዎችን በማፍራት ላይ እንደሚገኝ የኮሌጁ ዲን ዶክተር እስጢፋኖስ ዮሐንስ ገልጸዋል ። ኮሌጁ ለተመራቂዎቹ ሥራ እና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን ሲሰጥ መቆየቱ ነው የተገለጸው።
የኮሌጁ ዲን ዶክተር እስጢፋኖስ ዮሐንስ ኮሌጁ አሁንም በሚሰጠው ጥራት ያለው ትምህርት፣ የምርምር ሥራዎችንና የማኅበረሰብ አገልግሎት እየሰጠ በዘርፉ ተወዳዳሪና ተመራጭ ኮሌጅ በመሆን እየሠራ ነው ብለዋል።
ኮሌጁ በሬሚዲያል የትምህርት መርሐ ግብር ተማሪዎችን በማብቃት እና ከፍተኛ ውጤት እንዲያመጡ እና ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግባት የሚያስችላቸውን ውጤት እንዲያስመዘግቡ በማስቻል የበኩሉን ሚና መጫወቱንም ገልጸዋል።
በሥነ ሥርዓቱ ተመራቂዎች ቃለ መሐላ የፈጸሙ ሲሆን ሌሎች መርሐ ግብራት ተከናውነዋል።
በመጨረሻም በ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የደቡብ ጎንደር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተመራቂዎች በተማሩት ትምሕርት ወገናቸውን በትጋት እንዲያገለግሉ አደራ በማለት በጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተፈጽሟል።
የቅድስት ልደታ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ (ዶ/ር) ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ መልካም ፈቃድ በ1997 ዓ.ም በመቋቋመ የቤተክርስቲያናችን የትምሕርት ተቋም ነው።
©የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/