ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዕረፍታቸው በዓል መታሰቢያ በሸገር ሀገረ ስብከት በቡራዩ ጉጂ ገፈርሳ መልካ ኖኖ ክፍላተ ከተማ ፊሊ ዶሮ ደብረ ፀሐይ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተክርስቲያን ተከበረ።
ነሐሴ ፳፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ምየጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዓለ ዕረፍታቸው መታሰቢያ በሸገር ሀገረ ስብከት በቡራዩ ጉጂ ገፈርሳ መልካ ኖኖ ክፍላተ ከተማ ፊሊ ዶሮ ደብረ ፀሐይ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተክርስቲያን ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ተከበረ፡፡
ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሕይወታቸውን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ ይህንን ዓለም ንቀው በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና የኖሩ፣ እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሐዋርያ ናቸው፡፡
መልአከ ሕይወት ቆሞስ አባ ተክለ ወልድ ኃይለ ማርያም የቤተክርስቲያኑ አስተዳዳሪ እንደተናገሩት በደብሩ በርካታ የልማት ሥራዎች እተከናወኑ መሆኑን ገልጸው በዛሬው ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዓለ ዕረፍት ብፁዕነታቸው ተገኝተው በዓሉን አክብረው፣ ምእመናንን መባረካቸው እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል፡፡
ሊቀ ሥዩማን ዮሴፍ ፈቃደ እንደተናገሩት የክርስትና ሕይወት ጀምረን የምንተወው ሳይሆን እስከ መጨረሻው የምንጓዝበት ሕይወት ነው ብለዋል፡፡ ሊቀ ሥዩማን አያይዘውም ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በጾም፣ በጸሎት ተወስነው ሲጋደሉ፤ ከቊመት ብዛት የተነሣ አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች፡፡ ጻድቁ በአንድ እግራቸው ቆመው ያለ ምግብና ያለ ውኃ በትኅርምት ሌሊትና ቀን እንደ ምሰሶ ጸንተው በትጋት ወንጌል ለኢትዮጵያ ሕዝብ አስተምረዋል፡፡ እኛም የጻድቁን በረከት እንድናገኝ የተቸገረውን መርዳት፣ የተራበውን ማብላት፣ የተጠማውን ማጠጣት ይገባናል ብለዋል፡፡
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት መልእክት ጻድቁ አባታችን በሀገራችን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክና ተአምራትን በማድረግ ብዙ አሕዛብን ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር፤ ከገቢረ ኀጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ መልሰዋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናትንም አሳንጸዋል፡፡ እኛም ከጻድቁ በረከት ለማግኘት በዓሉን እያከበርን እንገኛለን ብለዋል፡፡
ብፁዕነታቸው አያይዘውም የጻድቅ መታሰቢያ በረከት ነው፤ ጻድቁ ከእግዚአብሔር በረከት አግኝተው ያረፉበትን በዓል እያከበርን ነው፤ በረከታቸው እንዲያድርብንም የጻድቁ ልጆች እውነተኛ መሆን አለብን፣ የእግዚአብሔር ምርጥ ዕቃ እንድንሆን በሰላም በፍቅር ሆነን ማገልገል አለብን ሲሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በአጠቃላይ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፤ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡ ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም የጻድቁን ሐዋርያዊ ውለታቸውን በማሰብና ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን ቅድስና መሠረት አድርጋ በስማቸው ጽላት ቀርጻ ስታከብራቸው ትኖራለች፡፡
በመርሐ ግብሩ ላይ መልአከ ኃይል አባ አፈወርቅ ዮሐንስ የመልካ ኖኖ፣ጉጂ ገፈርሳ ክፍለ ከተማና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የለሚ ኩራ ሥራ አስኪያጅን ጨምሮ በርካታ ምእመናን ተገኝተዋል፡፡
©የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/