የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ የአንድ ፐርሰንት ወርኃ መዋጮ አስመልክቶ የምስጋናና ዕውቅና መርሐ ግብር አካሔደ።
ጳጉሜን ፫/፳፻፲፰ ዓ/ምየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ በ2018 ዓ.ም የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያና ማጠናከሪያ የአንድ ፐርሰንት ወርሐዊ መዋጮ ገቢ አሰባሰብ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ ባለድርሻ አካላት የምስጋናና የዕውቅና መርሐ ግብር አካሂዷል።
በመርሐ ግብሩ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልእክት ወንጌል ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝበት መንገድ ስለሆነ ሁላችንም ለወንጌል ተደራሽነት የምናደረገዉን ጥረት ማጠናከር ይገባል ያሉ ሲሆን፤ ቤተክርስቲያን የምዕመናን ችግር አንደሌልባት ገልጸው ወንጌልን በዕውቀት በማድረስ ለተተኪዉ ትውልድ ልናተርፍ ይገባል ሲሉ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል።
በካፒታል ሆቴል በተካሄደው በዚህ መርሐ ግብር፣ የመምሪያውን የ2018 ዓ.ም. የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ኃላፊ መጋቢ ሐዲስ ጸጋ ወልደ ትንሳኤ አቅርበዋል።
እንደ መጋቢ ሐዲስ ፀጋ ገለጻ፣ በ2017 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት መምሪያው ራሱን ችሎ እንዲያስተዳድር ከተወሰነ በኋላ በ2018 ዓ.ም. ከእያንዳንዱ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ የሚሰበሰበውን አንድ ፐርሰንት ወርሐዊ መዋጮ በአግባቡ በማሰባሰብ ለመምሪያው ሥራዎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ተደርጓል።
በዓመቱ ከተከናወኑ ዋና ዋና ሥራዎች መካከል የሰው ኃይል ማደራጀት፣ የቢሮ ፓርቲሽን ማዘጋጀት፣ ከአህጉረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመወያየት የስብከተ ወንጌልን ተደራሽነት ማስፋፋት፣ በመምሪያው የተመሠረቱ ሚዲያዎችን ማጠናከር፣ ለሰባክያን ቤተ መጻሕፍትን ማደራጀት እና በ36 በተመረጡ አህጉረ ስብከት ልዩ ስምሪት ማካሄድ መቻሉን ገልጸዋል።
መምሪያው በቀጣይም የስብከተ ወንጌል ተደራሽነት አነስተኛ በሆነባቸው አህጉረ ስብከት ልዩ ስምሪት በማዘጋጀት ሥልጠናና የሕዝብ ጉባኤ ለማካሄድ፣ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጋር በመተባበር ሰባክያንን ለማሰልጠን፣ ሚዲያዎችን በማደራጀትና በማጠናከር በተለያዩ የሚዲያ ፕላትፎርሞች የስብከተ ወንጌልን ሥራ ለማስፋፋት ማቀዱንም አስታውቀዋል።
በመርሐ ግብሩ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ የውይይትና የአስተያየት መርሐ ግብሩን መርተዋል።። ንቡረ ዕድ ኤልያስ በመምሪያ ደረጃ የምስጋናና የዕውቅና መርሐ ግብር ማካሄድ የተለመደ ባለመሆኑ፣ እንደዚህ ያሉ ሠራተኞችንና ባለድርሻ አካላትን የሚያበረታቱ መርሐ ግብራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ገልጸዋል።
ከታችኛው የሥራ ክፍል ጋር በቀጥታ በመገናኘት ግብና ሐሳቦችን በመቀበል፣ ውይይትን በማጠናከርና ሐሳቦችን ወደ ዕቅድ በመቀየር ውጤታማ ሥራ ማከናወን እንደሚገባ አሳስበዋል። በተጨማሪም ዘመኑን የዋጀና በቂ መረጃን የያዘ ሪፖርት የሚዘጋጅበት ጊዜ ሩቅ እንዳልሆነ ገልጸው፣ የተጀመረው የሥራ አካሄድም ሊበረታታ እንደሚገባ አመልክተዋል።
መጋቤ ሐዲስ ሽፈራው እንዳሻው የመምሪያው ዋና ጸሐፊ በበኩላቸው “ስብከተ ወንጌልና አንድ በመቶ አስተዋጽኦ” በሚል ርዕስ ገለጻ አድርገዋል። በገለጻቸውም የወንጌል ማስፋፊያና ማጠናከሪያ አስተዋጽኦ ከብሉይ ኪዳን ዘመን ጀምሮ የነበረ፣ በክርስቶስና በሐዋርያት ዘመን የቀጠለ እና እስከ አሁን የደረሰ መሆኑን በመግለጽ የአንድ በመቶ ወርኃዊ አስተዋጽኦ ሚናንም አብራርተዋል።
በመጨረሻም በመርሐ ግብሩ ለ2018 ዓ.ም. የ1% ወርኃዊ መዋጮ ገቢ አሰባሰብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ ባለድርሻ አካላት የምስጋናና የዕውቅና ሽልማት በብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌል ና ሐዋርያዊ ተልዕእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ተበርክቷል።
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌል ና ሐዋርያዊ ተልዕእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ፣ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የከፋ፣ የሸካ፣ የቤንች ሸኮና የምዕራብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ እንጦስ የምዕራብ ሐረርጌ ሊቀ ጳጳስ፣ ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመንፈሳዊ ዘርፍ የምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነትና
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ ሐላፊዎች፣ የ8 ቱ ክፍላተ ከተማ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጆችና የመምሪያው ሠራተኞች በመርሐ ግብሩ ተሳትፈዋል።©የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ አገልግሎት/Addis Ababa Diocese Media Service